በአውስትራሊያ ነባር ዜጎች ዘንድ የድምፅ ለፓርላማ ፋይዳን አስመልክቶ የድጋፍና የተቃውሞ ድምፆች ቢስተጋቡም በአንድ የምርመር ሂደት በተሰበሰ የሕዝብ አስተያየት ግኝት መሠረት ድምፅ ለፓርላማ 80 ፐርሰንት የነባር ዜጎች ድጋፍ ያለው መሆኑ ተመልክቷል።
ትናንት ሐሙስ ጃኑዋሪ 26 በመላ አውስትራሊያ በተካሔደው የአውስትራሊያ ቀን ክብረ በዓልን በወረራ ቀንነት የተቃውሞ ድምፅ ለማሰማት በወጡ ነባር ዜጎች ዘንድ ክርክሮች ከአውስትራሊያ ቀን ይቀየር ወደ ድምፅ ለፓርላማ አዝምሞ ውሏል።
በመላ አገሪቱ በአሥር ሺህዎች የሚቆጠሩ የተቃውሞ ሰልፈኞች ድምፃቸውን ባሰሙባቸው የተለያዩ መድረኮች ተናጋሪ ከነበሩት ውስጥ አነስተኛ ቡድናት ቢሆኑም፤ ድምፅ ለፓርላማን አስመልክቶ የተቃውሞ ድምፃቸውን አሰምተዋል።
ይሁንና የነባር ዜጎች ጤና ተሟጋችና የሥራ ግብረ ኃይል አባል የሆኑት ፓት አንደርሰን 'ምንም እንኳ አናሳና ጯሂ ድምፆች ጎልተው ቢሰሙም ድምፅ ለፓርላማ የ80 ፐርሰንት ነባር ዜጎች የድጋፍ ድምፅ አለው' ሲሉ አመላክተዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትር አንቶኒ አልባኒዚም በበኩላቸው፤ ድምፅ ለፓርላማን አስመልክቶ ሕዝበ ውሳኔ ከመካሔዱ በፊት ከአውስትራሊያውያን ጋር ምክክር ማድረጉና መረጃዎችን መለዋወጡ እንደሚቀጥል አሳሰበዋል።
አቶ አልባኒዚ ለነባር ዜጎች ዕውቅናን የመቸሩ ዕሳቤ የተጀመረው ባለፈው ክፍለ ዘመን መሆኑን አስታውሰው፤
አውስራሊያውያን መረጃዎችን የሚያገኙበትና ድምፅ በመስጠትም ዕርቅን ወደፊት የሚያራምዱበት ጊዜ ስለመኖሩ ተናግረዋል።
የድምፅ ለፓርላማ ሕዝበ ውሳኔ በዚህ ዓመት አጋማሽ ላይ ይካሔዳል ተብሎ ይጠበቃል።
ገዲብ የእስላማዊ መንግሥት መሪ
የዩናይትድ ስቴትስ ባለስልጣን የአሜሪካ ልዩ የዘመቻ ኃይል ሶማሊያ ውስጥ አንድ ገዲብ የእስላማዊ መንግሥት መሪና 10 ሚሊሺያዎችን መደምሰሱን አስታወቁ።
እንደ አንድ የዩናይትድ ስቴትስ አፍሪካ ዕዝ ባለስልጣን ገለጣ፤ የዩናይትድ ስቴትስ ጦር "ሶማሊያ ውስጥ ባካሔደው ስኬታማ ፀረ ሽብር ዘመቻ" ለአፍሪካና አፍጋኒስታን እስላማዊ መንግሥት የገንዘብ ስብሰባና ድጎማ ቁልፍ አስተባባሪ የነበረውን ቢላል አል-ሱዳኒንን ለመግደል በቅቷል።
በዘመቻው ሂደትም የአንድም ሰላማዊ ወይም ወታደር ሕይወት እንዳልጠፋም ተገልጧል።
ዘመቻው እንዲከናወን በዚህ ሳምንት መጀመሪያ ላይ ትዕዛዝ የሰጡት የዩናይትድ ስቴትስ ፕሬዚደንት ጆ ባይደን ናቸው።